Site icon ethioelection.com

የምርጫ የማዘዣ ማዕከል ሊቋቋም ነው

ምርጫ ቦርድ የቀጣዩ ምርጫ ደህንነትን ለማረጋገጥ በራሱ የሚመራ እና 27 አባላት የሚኖሩት የጋራ የምርጫ የማዘዣ ማዕከል (Joint Election Operation Center – JEOC) በፌደራል ደረጃ ለማቋቋም እቅድ እንዳለው አስታውቋል። በእቅዱ ላይ ምክክር ይደረግበታል ተብሏል።

ማዕከሉን የመመስረት እቅድ ይፋ ያደረጉት የምርጫ ቦርድ አባል ዶ/ር ጌታሁን ካሳ ናቸው። ዶ/ር ጌታሁን የካቲት 6 በተካሄደ ኮንፍረንስ ላይ እንደተናገሩት ቦርዱ “በምርጫ ሂደት ውስጥ የሚታየው ስጋት (risk) ምንድነው?” የሚለውን የተመለከተ ጥናት በሁለት ዙር አካሂዷል። የዳሰሳ ጥናቱ ወደፊትም በየጊዜው እንደሚቀጥል ጠቁመዋል። 

የቀድሞው የአየር ኃይል አዛዥ ሜጀር ጄነራል አለምሸት ደግፌ ባለፈው መስከረም ወር በተደረገ አንድ ኮንፍረንስ ላይ የጸጥታ ጉዳዮችን የሚከታተል የምርጫ ማዕከል የማቋቋም አስፈላጊነትን አንስተው ነበር።  ምርጫው ይሳካ ዘንድ “የምርጫ ጸጥታ ማስከበሪያ ማዕከል” ማቋቋም እንደሚሻል መክረዋል።  

በምርጫ ወቅት ሰላም እና ጸጥታን ለማረጋገጥ መወሰድ ስለሚገባቸው እርምጃዎች ገለጻ ያደረጉት ሜጀር ጄነራል አለምሸት በኢትዮጵያ “የጦር መሳሪያ ዝውውር በጣም ከልኩ ያለፈ ነው” ሲሉ አሳሳቢነቱን ጠቅሰዋል። በመጪው ምርጫ የጸጥታ ችግር መንስኤ ሊሆኑ ይችላሉ ካሏቸው ውስጥ “የታጠቁ የፖለቲካ ኃይሎች” ይገኙበታል። የታጠቁ ኃይሎች “ህዝብ ውስጥ እንዲንቀሳቀሱ በማድረግ ነጻ ምርጫ የሚባል ነገር ሊደረግ አይችልም” ብለዋል።

በየካቲት 6 ኮንፍረንስ ላይ የተገኙት የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር እንደሻው ጣሰው ለምርጫ “ሰራዊታችንን በአግባቡ እናሰለጥናለን። የተለያዩ ችግሮች ቢያጋጥሙ እንዴት መከላከል እንደሚቻል በቂ ዝግጅቶች አድርገናል” ብለዋል። “በከተማም ሆነ በገጠር ሽፍታ ካለ አንቀበልም። ህግ እናስከብራለን” ሲሉ አስጠንቅቀዋል። 

Exit mobile version