የምርጫ ካርታ በመጪው ወር ይፋ ይደረጋል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም በምርጫ ጣቢያነት ያገለገሉ ቦታዎችን ለመለየት የጂ.ፒ.ኤስ ቴክኖሎጂን እየተጠቀመ ይገኛል። በመስሪያ ቤቱ ባለሙያዎች የተዘጋጀው የምርጫ ጣቢያዎች ካርታ በቅርቡ ለቦርዱ ውሳኔ ይቀርባል ተብሏል። 

ቦርዱ ነሐሴ 23 ለሚካሄደው ሀገራዊ  ምርጫ እስከ 48 ሺህ የምርጫ ጣቢያዎች እንደሚኖሩ ቀደም ሲል አስታውቆ ነበር። ምርጫ ቦርድ የየምርጫ ጣቢያዎቹን ወሰን የመለየት ስራን በቴክኖሎጂ በመታገዝ ለወራት ሲያካሂድ መቆየቱን በቅርቡ ገልጿል። በአዲስ አበባ የሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎችን የጂ.ፒ.ኤስ መረጃ ለማሰባሰብ ብቻ 20 ቀናት መውሰዱን የቦርዱ ባለሙያዎች አስረድተዋል። 

ከዘንድሮው ምርጫ በፊት በተካሄዱ አምስት ምርጫዎች ወቅት የምርጫ ክልሎችን እና የምርጫ ጣቢያዎችን የሚገልፅ ካርታ አልነበረም።  የምርጫ ጣቢያዎች የሚታወቁት በስም እና በቁጥር ብቻ እንደነበር ባለሙያዎቹ ይናገራሉ።

ይህ አሰራር ምርጫ ለማካሄድ፣ አዳዲስ ምርጫ ጣቢያዎችን ለመክፈት እንዲሁም ሎጅስቲክስ እና ቁሳቁስ ለማሰራጨት አስቸጋሪ አድርጎት እንደነበር ባለሙያዎቹ ያብራራሉ። እነዚህን ችግሮች ይፈታል የተባለለት አዲሱ የምርጫ ካርታ በመጪው የመጋቢት ወር መጀመሪያ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል።


Leave a Reply