Site icon ethioelection.com

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ከተባባሰ በመጪው ምርጫ ዕጣ ፈንታ ላይ ውሳኔ እንደሚተላለፍ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ተናገሩ

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ችግር ለተራዘመ ጊዜ የሚቀጥል ከሆነ እና በምርጫ ቦርድ ስራ ላይ እንቅፋት ከፈጠረ የመጪው ምርጫን ዕጣ ፈንታ ለመወሰን ውይይት እንደሚካሄድ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን የተናገሩት የኮሮና ቫይረስን አስመልክቶ ዛሬ አመሻሽ ላይ በሰጡት መግለጫ ነው። 

የኮሮና ቫይረስ በመጪው ምርጫ ላይ ተጽዕኖ ያሳድር እንደው ለመለየት ምርጫ ቦርድ የራሱን ጥናት እየሰራ እንደሚገኝ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የቦርዱን ጥናት መሰረት አድርጎ ውሳኔ እንደሚተላለፍ አመልክተዋል። የመጨረሻ ውሳኔው ይፋ የሚደረገውም “የጋራ ስምምነት” ከተደረሰበት በኋላ እንደሚሆን በሀገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ “በሰበር ዜና” በተላለፈው መግለጫቸው አስታውቀዋል። 

“በቻይና እንዳየነው አይነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሄንን ጉዳይ መቆጣጠር፣ ማለፍ የሚቻል ከሆነ በአሰብነው እቅድ መሰረት መሄዱ ተመራጭ ቢሆንም ምናልባት ለተራዘመ ጊዜ ችግሩ የሚቀጥል ከሆነ እና ምርጫ ቦርድ ስራውን መከወን የሚቸገር ከሆነ፤ በሚያደርጉት ጥናት መሰረት ውይይት የሚደረግ ይሆናል” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። 

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በሀገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ “በሰበር ዜና” በተላለፈው መግለጫቸው የኮሮና ቫይረስ በምርጫ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖን በተመለከተ ምርጫ ቦርድ የራሱን ጥናት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።  የቦርዱን ጥናት መሰረት አድርጎም ውሳኔ እንደሚተላለፍ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ምሽቱን ባወጣው መግለጫ የኮሮና ቫይረስ ለሳምንታት አሁን ባለበት ሁኔታ ከቀጠለ በምርጫ ኦፕሬሽን ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ማረጋገጫ ሰጥቷል። ምርጫ ቦርድ በቫይረስ ምክንያት ተጽዕኖ ሊደርስባቸው ያላቸው “ከፍተኛ የሰው ዝውውር ያሳትፋሉ” በሚል የገለጻቸውን “የመራጮች ትምህርት፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች ስልጠና እና የቁሳቁስ ስርጭትን” ነው። 

በእነዚህ ተግባራት ላይ የሚደርስ መስተጓጎል በመራጮች ምዝገባ ዝግጅት ላይ ተጽእኖ እንደሚያስከትል ቦርዱ ዛሬ ለውይይት ለጠራቸው የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ገለጻ አድርጓል።  ገዢው የብልጽግና ፓርቲን ጨምሮ 45 የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደተሳተፉበት በተገለጸው በዚህ ውይይት የኮሮና ቫይረስ በምርጫ ኦፕሬሽን ስለሚኖረው ተጽዕኖ እና ሊወሰዱ ስለሚችሉ አማራጭ እርምጃዎች ውይይት መደረጉን ቦርዱ አስታውቋል።

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ  በምርጫው ዝርዝር አፈጻጸም እና በጊዜ ሰሌዳው ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ ለመገምገም፤ ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር ተከታታይ ውይይት በቀጣይም እንደሚያደርግ ቦርዱ ገልጿል። (ኢትዮኢሌክሽን) 

Exit mobile version