Explainers

የፓርላማ መቀመጫዎች ስብጥር

አሁን በስራ ላይ ያለው የኢትዮጵያ ህገ መንግስት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ቁጥር ከ550 እንዳይበልጥ ይደነግጋል ። በየአምስት ዓመት በሚካሄድ ምርጫ የሚመረጡት የምክር ቤቱ አባላት ዘጠኝ ክልሎች እና ሁለት የከተማ መስተዳድሮችን የሚወክሉ ናቸው። 

ከፓርላማ መቀመጫዎች አብላጫውን ቁጥር የሚይዙት የኦሮሚያ ክልል ተመራጮች ናቸው። ኦሮሚያ 178 የተወካዮች ምክር ቤት አባላትን ያስመርጣል። በመቀመጫ ብዛት ሁለተኝነትን የያዘው የአማራ ክልል በበኩሉ በፌደራል ፓርላማ በ138 ተመራጮች ይወከላል። 

ሃምሳ ስድስት ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ህዝቦችን በውስጡ ያቀፈው የደቡብ ክልል የፓርላማውን ሶስተኛ ከፍተኛ ቁጥር ይዟል። ክልሉ በተወካዮች ምክር ቤት 123 አባላት አሉት። የትግራይ ክልል በፌደራሉ ፓርላማ 38 መቀመጫዎች በመያዝ በተወካዮች ብዛት በአራተኛነት ደረጃ ተቀምጧል። 

ሶማሌ ክልል እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በፓርላማ ያላቸው መቀመጫ ብዛት እኩል ነው። ሁለቱም በተመሳሳይ 23 ተወካዮች በፌደራሉ የእንደራሴዎች ምክር ቤት አሏቸው። የታዳጊ ክልል የሚባሉት ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ አፋር እና ጋምቤላ ክልሎች በድምሩ ያላቸው የፓርላማ ተወካዮች ብዛት ከሶማሌ ክልልም ሆነ ከአዲስ አበባ ያንሳል። ሶስቱ ክልሎች በድምሩ በፓርላማ የሚወከሉት በ20 ተመራጮች ነው። 

እንደ አዲስ አበባ ሁሉ የከተማ አስተዳደርነት እውቅና ያለው የድሬዳዋ ከተማ ሁለት ተመራጮች ብቻ ለፓርላማ ይልካል። የድሬዳዋ አጎራባች የሆነው የሀረሪ ክልልም በፓርላማ ያሉት የተወካዮች ቁጥር ብዛት ሁለት ብቻ ነው። (ኢትዮኢሌክሽን)  


የዱባዩ የምርጫ ሰነዶች እና ቁሳቁሶች ህትመት ምን ይለየዋል?

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ነሐሴ 23 ለሚያካሄደው ምርጫ የሚያገለግሉ ሰነዶች እና ቁሳቁሶች ከሀገር ውጪ ማሳተም ጀምሯል። የምርጫ ሰነዶችን ህትመት የሚያካሂደው  “አል-ጉህሬር” የተባለ በዱባይ የሚገኝ ማተሚያ ቤት ነው።

የምርጫ ሰነዶች እና ቁሳቁሶች ህትመት የተጀመረው ባለፈው ታህሳስ ወር ነበር። የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ እና ምክትላቸው ውብሸት አየለ ለኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ማላዊ እና ዛምቢያ የምርጫ ቁሳቁሶችን እንዳተመ የተነገረለትን የዱባዩ ማተሚያ ቤትን በወቅቱ ስፍራው ድረስ በመጓዝ ጎብኝተዋል። የማተሚያ ቤቱንም ኃላፊዎችም አግኝተው አነጋግረዋቸዋል።

የምርጫ መዛግብቱ እና ሰነዶቹ በአማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ትግርኛ፣ ሶማሊኛ እና አፋርኛ ቋንቋዎች እንደሚታተሙ ምርጫ ቦርድ ገልጾ ነበር። ለመራጮች ምዝገባ የሚደረገው የሰነድ ዝግጅት መጠባበቂያን ጭምር እንደሚያካትት ቦርዱ ጨምሮ ገልጿል። 

ምርጫ ቦርድ የዱባዩ ህትመት የመራጮች ምዝገባን ዘመናዊ እና ተዓማኒ እንደሚያደርግ ጠቁሟል። ህትመቱ የምርጫው ሂደት አለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ እና አዲሱ የምርጫ ህግ ላይ የተቀመጡትን መስፈርቶች ያሟላ እንዲሆን የሚያስችል ነውም ተብሏል። ከዚህ በተጨማሪም ሊፈጠሩ የሚችሉ ስህተቶችን ለመቀነስና እና ማጭበርበርን ለማስወገድ እንደሚረዳ ተገልጿል።

ህትመቱ ከዚህ ቀደም በሀገር ውስጥ ሲከናወን ከነበረው ምን እንደሚለየው ለመረዳት ዝርዝሩን ከስዕላዊ መረጃው ይመልከቱ።

(ኢትዮኢሌክሽን)