የአውሮፓ ህብረት ለመጪው ምርጫ የታዛቢ ቡድን እንደሚልክ ማረጋገጫ ሰጠ

የአውሮፓ ህብረት ዘንድሮ በኢትዮጵያ ለሚካሄደው ምርጫ የታዛቢዎች ቡድን እንደሚልክ አስታወቀ። ህብረቱ የታዛቢ ቡድኑን ወደ ኢትዮጵያ እንደሚልክ ዛሬ ማረጋገጫ የሰጡት የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ጆሴፕ ቦሬል ናቸው። 

ከአፍሪካ ህብረት ኃላፊዎች ጋር ለመወያየት ከ20 የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽነሮች ጋር ወደ አዲስ አበባ የመጡት ቦሬል ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋርም ተገናኝተዋል። በአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳዮችን እና የጸጥታ ፖሊሲን በኃላፊነት የሚመሩት ቦሬል ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በነበራቸው ቆይታ ከተነሱ አንኳር ጉዳዮች ውስጥ ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት የምታካሄደው ምርጫ ይገኝበታል።  

ምክትል ፕሬዝዳንቱ ከውይይቱ በኋላ በግል የትዊተር ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት “በኢትዮጵያ ዲሞክራሲን እና መረጋጋትን ለማጠናከር መጪው ምርጫ ሁነኛ መፈተሻ ነው” ብለዋል። በዚሁ መልዕክታቸውም የህብረቱ ታዛቢ ቡድን በመጪው ነሐሴ የሚካሄደውን ምርጫ እንደሚታዘብ ይፋ አድርገዋል። 

የአውሮፓ ህብረት የዘንድሮውን ምርጫ እንዲታዘብ ከኢትዮጵያ መንግስት ባለፈው ታህሳስ ወር ይፋዊ ግብዣ እንደደረሰው ቀደም ሲል አስታውቆ ነበር። ይህንን ተከትሎም ህብረቱ የቅድመ ምርጫ ጥናት ቡድን ባለፈው ወር ወደ ኢትዮጵያ ልኳል። ቡድኑ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በመዘዋወር ለሁለት ሳምንታት ጥናት ሲያካሂድ የቆየ ሲሆን የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ ከተለያዩ አካላት ጋር ተነጋግሯል። 

የቅድመ ምርጫ ጥናት ቡድኑ በሀገሪቱ ያለውን የጸጥታ ሁኔታ መገምገሙን ቡድኑን መርተው ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የነበሩት ሎይክ ዲፋዬ ገልጸው ነበር። ከዚህ በተጨማሪም የሎጀስቲክ እና የትራንስፖርት ጉዳዮችን መመልከታቸውን አስረድተዋል። ዲፋዬ “የታዛቢዎች ቡድንን በተመለከተ ዋናው መሰረታዊ መስፈርት የቡድኑ ጠቃሚነት ነው። ለመጪው ምርጫ ተጨማሪ እሴት ይኖረዋልን?” ሲሉ “ቁልፉ ነገር ሂደቱ” መሆኑን አጠይቀው ነበር። 

Leave a Reply