Tag: Election Board Ethiopia

አማራጭ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳዎችን የያዘ የዳሰሳ ጥናት ለፓርላማ ተላከ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መጪው ምርጫ ሊካሄድባቸው የሚችልባቸውን ሁለት አማራጭ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳዎችን ያካተተ የዳሰሳ ጥናት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ላከ። የጊዜ ሰሌዳዎቹ መጪው ምርጫ በታህሳስ አሊያም በየካቲት የመካሄድ ዕድል እንዳለው ጥቆማ ሰጥተዋል።

ምርጫ ቦርድ ባለፈው ማክሰኞ፤ መጋቢት 22፤ ባወጣው መግለጫ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት፤ የተወካዮች ምክር ቤት የስልጣን ዘመን ከማብቃቱ በፊት ምርጫ ማካሄድ እንደማይችል አሳውቆ ነበር። ምክር ቤቱ የስልጣን ጊዜውን አስመልክቶ ውሳኔ የሚያሳልፍ ከሆነ ለዚያ ይረዳው ዘንድ ቦርዱ ያደረገውን የዳሰሳ ጥናት ለፓርላማው እንዲተላለፍ ውሳኔ አስተላልፎ ነበር።

በ28 ገጾች የተዘጋጀው እና “ኢትዮ ኢሌክሽን” የተመለከተችው ይህ የዳሰሳ ጥናት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በመጪው አጠቃላይ ምርጫ ላይ የሚኖረውን አሉታዊ ተጽዕኖ የተነተነ ነው። ጥናቱ የቢሆን ሁኔታ ግምቶች (scenarios) ላይ በመመስረት የምርጫ የጊዜ ሰሌዳን እና የምርጫ ኦፕሬሽንን ከልሶ፣ ስራውን እንደገና ማስጀመር የሚቻልባቸው አማራጭ የእቅድ አፈጻጸሞችን በዝርዝር አስቀምጧል። በምርጫ ቦርድ አማካሪ ባለሙያዎች ተሰርቶ የቀረበው ጥናቱ ሁለት የቢሆን ሁኔታ ግምቶችን በዋናነት አስቀምጧል። 

የመጀመሪያው የቢሆን ሁኔታ ግምት የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በኢትዮጵያ መንግስት እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎች ለአራት ሳምንታት ብቻ እንደሚቆዩ ታሳቢ ያደረገ ነው። እርምጃዎቹ የመራጮች ምዝገባን ቢያንስ በአራት ሳምንታት ሊያዘገዩት እንደሚችሉ ሆኖም ምርጫውን አስቀድሞ በተያዘለት ቀን ማከናወን እንደሚቻል የጠቆመ ነበር። 

ይህ አካሄድ የምርጫውን ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ ከመክተቱም ባሻገር የመራጮች እና አጠቃላይ የህብረተሰቡን ተሳትፎ በከፍተኛ ሁኔታ ሊቀንስ እንደሚችል የዳሰሳ ጥናቱ አመላክቷል። በዚህ ጊዜ ለምርጫ ኦፕሬሽን ድጋፍ የሚያደርጉ ተቋማትን የተሟላ ድጋፍ ማግኘት አስቸጋሪ እንደሚሆንም ጥናቱ ጠቅሷል። 

ቦርዱ “የወረርሽኙ ስጋት ተወግዶ ሁኔታዎች ሲመቻቹ፣ በድጋሚ ግምገማ በማድረግ፣ አዲስ የምርጫ ኦፕሬሽን እቅድ እና ሰሌዳ በማውጣት እንቅስቃሴውን የሚያስጀምር ይሆናል” ሲል በማክሰኞው ውሳኔው ላይ ጠቁሟል።

ሁለተኛው የቢሆን ሁኔታ ግምት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር የኢትዮጵያ መንግስት የሚወስዳቸው እርምጃዎች “ከሚያዚያ 7 ቀን 2012 ዓ.ም በኋላም ሊቆዩ ይችላሉ” በሚል የተዘጋጀ ነው። በየጊዜው የሚወሰዱት እርምጃዎች በዚሁ ከቀጠሉ፤ ምርጫ ቦርድ አስቀድሞ ባወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት፤ ምርጫውን ማስፈጸም እንደማይችል ያስጠነቀቀም ነበር። 

ምርጫ ቦርድ መጪውን ምርጫ በተመለከተ ባለፈው ማክሰኞ፤ መጋቢት 22፤ ይፋ ያደረገው ውሳኔ ሁለተኛውን የቢሆን ሁኔታ የተንተራሰ ነው። ውሳኔው መጪው ምርጫ በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት በታቀደለት ጊዜ መከናወን እንደማይችል ያሳወቀ ነበር። ቦርዱ የዘንድሮውን አጠቃላይ ምርጫ ነሐሴ 23 ለማካሄድ አቅዶ የነበረ ቢሆንም በወረርሽኙ ምክንያት ከወር በፊት ያወጣውን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ መሰረዙን ገልጿል። በጊዜ ሰሌዳው የታቀዱ የምርጫ ተግባራት ለጊዜው እንዲቆሙም ውሳኔ አሳልፏል። 

ቦርዱ “የወረርሽኙ ስጋት ተወግዶ ሁኔታዎች ሲመቻቹ፣ በድጋሚ ግምገማ በማድረግ፣ አዲስ የምርጫ ኦፕሬሽን እቅድ እና ሰሌዳ በማውጣት እንቅስቃሴውን የሚያስጀምር ይሆናል” ሲል በማክሰኞው ውሳኔው ላይ ጠቁሟል። የዳሰሳ ጥናቱ በበኩሉ የምርጫ ሰሌዳን ለመቀየር እና የምርጫ ተግባራትን ድጋሚ ለማስጀመር፤ የፌደራል እና የክልል የመንግስት ተቋማት ሙሉ የስራ አቅማቸውን የሚያገኙበትን ሁኔታ ከግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚያስፈልግ ይመክራል።  

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል በፌደራል እና የክልል መንግስታት የተላለፉ ክልከላዎች እና ገደቦች በዝናብ ወቅት የሚነሱ ከሆነ “በሃገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ላይ እንደሚኖር ከሚጠበቀው ከባድ ዝናብ የተነሳ ይህን የማከናወኛ ጊዜ ረጅም ሊሆን እንደሚችል ይጠበቃል” ይላል ጥናቱ። ገደቦቹ ከሰኔ እስከ ሐምሌ ባሉት ወራት የሚነሱ ከሆነ ወደ ሙሉ ተቋማዊ አቅም ለመመለስ የአንድ ወር የዝግጅት ጊዜ እንደሚያስፈልግ ጥናቱ አመልክቷል። 

በዚህ የቢሆን እውነታ ላይ በመመርኮዝ በጥናቱ የተካተተ አማራጭ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ግንቦት 24፤ 2012ን እንደ መነሻ ቀን ወስዷል። በጊዜ ሰሌዳው መሰረት መጪው ምርጫ በታህሳስ 19 ቀን 2013 መካሄድ ይችላል።

የመራጮች ምዝገባ ከነሐሴ 27 እስከ መስከረም 22፤ 2013 ድረስ መደረግ እንደሚችል የሚጠቁመው ይህ የጊዜ ሰሌዳ የምረጡኝ ዘመቻው ከመስከረም 20፤ 2013 ጀምሮ ባሉት 89 ቀናት ውስጥ እንዲከናወን አማራጭ ሀሳብ አስቀምጧል። በጊዜ ሰሌዳው መሰረት ምርጫ ቦርድ የተረጋገጠ የምርጫ ውጤት እንዲያሳውቅ የሚጠበቀው ከታህሳስ መጨረሻ እስከ ጥር 8፤ 2013 ባሉት ቀናት ይሆናል።

የቦርዱ የዳሰሳ ጥናት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭትን ለመግታት የተጣሉት ገደቦች የሚነሱት ከነሐሴ እና እስከ መስከረም ባሉት ወራት ውስጥ ከሆነ በሚል ሌላ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳም በአማራጭነት አቅርቧል። በዚህኛው የምርጫ ሰሌዳ መሰረት መራጮች ድምጻቸውን የሚሰጡበት ዕለት የካቲት 21፤ 2013 እንዲሆን ታስቧል።

የተረጋገጠ የምርጫ ውጤት ይፋ የሚደረገው በመጋቢት ወር ባሉት የመጀመሪያ 10 ቀናት ውስጥ ነው። ጥቅምት 24፤ 2013 እንዲጀመር የታቀደው የመራጮች ምዝገባ ክንውን ለአንድ ወር የሚቆይ ሲሆን የምረጡኝ ዘመቻ ከህዳር 22 እስከ ጥር 24፤ 2013 ይካሄዳል። 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በየካቲት ወር ያወጣውን የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ቢሰርዝም ወደፊት ለሚያወጣው አዲስ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ እንዲሁም ምርጫውን ለማስፈፀም የሚደረጉ ዝግጅቶችን ካቆሙበት ለማስቀጠል የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚቆይ በዳሰሳ ጥናቱ ተመልክቷል። ቦርዱ የኮሮና ወረርሽኝን ለመከላከል ለአስቸኳይ ስራ ከሚፈለጉ ሰራተኞች በስተቀር ሌሎች ሰራተኞቹ ከመኖሪያ ቤታችው ሆነው እንዲሰሩ አድርጓል። በዚህም ምክንያት ተጨማሪ ውሳኔዎች እስኪተላለፉ ድረስ ቦርዱ በዝቅተኛ አቅሙ ስራዎችን እንደሚያከናውን በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡ (ኢትዮ ኢሌክሽን)

መጪው ምርጫ በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት በታቀደለት ጊዜ እንደማይካሄድ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በህገ መንግስቱ በተቀመጠው መሰረት መጪውን አጠቃላይ ምርጫ ማድረግ የማይችል መሆኑን አስታወቀ። የተወካዮች ምክር ቤት ሁኔታውን ተገንዝቦ ውሳኔ እንዲያሳልፍም ጠይቋል።

ምርጫ ቦርድ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በምርጫ 2012 ኦፕሬሽን ላይ የፈጠረውን ችግር ከገመገመ በኋላ ባሳለፈው ውሳኔ ባለፈው የካቲት ወር ያወጣውን የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረዙን ምሽቱን ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል። በጊዜ ሰሌዳው የታቀዱ ተግባራትም ለጊዜው እንዲቆሙ መወሰኑንም ገልጿል።

በቦርዱ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት መራጮች ድምጽ የሚሰጡበት ቀን ነሐሴ 23 ቀን 2012 እንዲሆን ታቅዶ ነበር። ቦርዱ ከምርጫው ማግስት አንስቶ እስከ ጳጉሜ 3 ድረስ የተረጋገጠ ውጤት ይፋ እንደሚያደርግ በጊዜ ሰሌዳው ማስቀመጡ ይታወሳል።

በተለምዶ በግንቦት ወር ይካሄድ የነበረው አጠቃላይ ምርጫ ወደ ነሐሴ ወር የተገፋው በአዲስ አወቃቀር እና አባላት የተቋቋመው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለመጪው ምርጫ “በቂ የዝግጅት ጊዜ እንዲያገኝ” በሚል ነበር። ምርጫው በክረምት ወር እንዲደረግ መወሰኑን ተከትሎ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተቃውሟቸውን ሲያሰሙ ቆይተዋል። 

ምርጫ ቦርድ በበኩሉ መጪውን ምርጫ ከነሐሴ ወር ወዲያ ባሉት ጊዜያት ለማከናወን የማይችለው በኢትዮጵያ ህገ መንግስት በተቀመጠ ገደብ ምክንያት መሆኑን ምላሽ ሰጥቶ ነበር። ቦርዱ በዛሬው መግለጫውም ይህን የህገ መንግስት የጊዜ ገደብ አንስቷል። 

በስራ ላይ የሚገኘው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስልጣን ጊዜው ከሚያበቃበት አንድ ወር አስቀድሞ ቦርዱ መጪውን አጠቃላይ ምርጫ ማድረግ እንደሚኖርበት መግለጫው አስታውሷል። ቦርዱ ባወጣው የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ የተገለጹ ተግባራትን በተያዘላቸው ጊዜ መሰረት እንዳያከናውን ግን የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ እንቅፋት እንደሆነበት ገልጿል። በዚህም ምክንያት ምርጫውን በእቅዱ መሰረት ማድረግ እንደማይችል አስታውቋል።

የተወካዮች ምክር ቤት አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ተገንዝቦ ውሳኔ መስጠት ያስችለው ዘንድ ቦርዱ በዛሬው ዕለት ያሳለፈውን ውሳኔ ዝርዝር ለምክር ቤቱ  እንደሚያስተላልፍ ገልጿል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተጠሪነቱ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መሆኑ ይታወቃል። ምክር ቤቱ በኮሮና ቫይረስ ስጋት ሳቢያ መደበኛ ስብሰባዎቹን ላልተወሰነ ጊዜ እንደማያደርግ ከሁለት ሳምንት በፊት አስታውቆ ነበር። (ኢትዮ ኢሌክሽን)

የምርጫ ቦርድ የውጭ ሀገር ሰራተኞች በኮሮና ወረርሽኝ ስጋት ወደ ሀገራቸው ተመለሱ

ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቴክኒክ ድጋፍ የሚሰጡ በርካታ የውጭ ሀገር ሰራተኞች በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት ምክንያት ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውን የመስሪያ ቤቱ ምንጮች ገለጹ። በሀገር ውስጥ የቀሩትም ቢሆኑ በቤታቸው እንዲሰሩ ድርጅቶቻቸው ውሳኔ ማሳለፋቸው ታውቋል። 

ምን ያህል የውጭ ሀገር ሰራተኞች እስካሁን ወደ ሀገራቸው እንደተመለሱ አጠቃላይ መረጃ በመጠናቀር ላይ መሆኑን የተናገሩት የቦርዱ የ“ኢትዮኢሌክሽን” ምንጭ፤ ሆኖም ቁጥራቸው “በርካታ” የሚባል እንደሆነ አስረድተዋል። “የተወሰኑቱ ሀገር ለቅቀው ሄደዋል” የሚሉት እኚሁ ምንጭ “ሌሎቹ ወደ የሀገራቸው የሚወስዳቸው በረራ ለማግኘት በመቸገራቸው አሁንም ለመሄድ በጥረት ላይ ናቸው” ብለዋል። 

ለምርጫ ቦርድ በቀጥታ ስራ ከሚሰሩ ከእነዚህ ቁልፍ ሰራተኞች በተጨማሪ በየዓለም አቀፍ ተቋማቱ   ከምርጫ ጋር የተያያዘ ስራ የሚሰሩ ሰራተኞች በቤታቸው ሆነው እንዲሰሩ መወሰኑን ለ“ኢትዮኢሌክሽን” የደረሰው መረጃ ያመለክታል። ምርጫ ቦርድም  “አጋሮቼ” ብሎ የሚጠራቸው ዓለም አቀፍ ተቋማት በበሽታው ስጋት ምክንያት የየራሳቸውን እርምጃ መውሰድ መጀመራቸውን አስታውቋል። 

ምርጫ ቦርድ ይህን የገለጸው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በመጪው ምርጫ ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ በተመለከተ ባለፈው ሳምንት ባሰራጨው የግምገማ ሰነድ ላይ ነው። እርምጃዎቹ ተቋማቱ ለመጪው ምርጫ ሊያበረክቱት በሚችሉት የቴክኒካዊ እና የገንዘብ ድጋፍ ላይ “ጉልህ ተጽዕኖ ይኖራቸዋል” ብሏል ሰነዱ።

በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት “ለኢትዮጵያ ምርጫ የሚደረገው ዓለም አቀፍ ድጋፍ በከፍተኛ ሁኔታ ሊቀንስ ይችላል” ሲል ምርጫ ቦርድ ስጋቱን ገልጿል 

ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ ለ45 የፖለቲካ ፓርቲዎች ተወካዮች ቀርቦ ምክክር በተደረገበት በዚህ ሰነድ ላይ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ቦርዱ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ቃል የተገባለትን ገንዝብ የማግኘት ችግር ሊገጥመው እንደሚችል ተጠቁሟል። “አሁን ያለው ዓለም አቀፍ የጤና ቀውስ ከግምት ከገባ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለምርጫዎች ድጋፍ የተመደበው ገንዘብ ለሰብዓዊ እና የጤና ድጋፍ የመዛወር እድሉ ከፍ ያለ ነው” በማለት ስጋቱን ያስቀመጠው የቦርዱ ሰነድ “በዚህ ምክንያትም ለኢትዮጵያ ምርጫ የሚደረገው ዓለም አቀፍ ድጋፍ በከፍተኛ ሁኔታ ሊቀንስ ይችላል” ሲል ያስጠንቅቃል። 

ምርጫ ቦርድ ነሐሴ 23 እንዲካሄድ ቀን የተቆረጠለትን የዘንድሮ ምርጫ ለማካሄድ 3.5 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ ቀደም ብሎ አስታውቆ ነበር። የፌደራል መንግስት ለቦርዱ የምርጫ ኦፕሬሽን እና ሎጀስቲክ ስራ ማከናወኛ የመደበው ገንዘብ ግን 2.25 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው። ቀሪውን ገንዘብ ከዓለም አቀፍ ማህብረሰብ በሚገኝ ድጋፍ ለመሸፈን ላቀደው ምርጫ ቦርድ ከተለያዩ ሀገራት እና ተቋማት የ40 ሚሊዮን ዶላር ያህል የገንዘብ ድጋፍ ቃል ተገብቶለት ነበር።  (ኢትዮኢሌክሽን) 

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ከተባባሰ በመጪው ምርጫ ዕጣ ፈንታ ላይ ውሳኔ እንደሚተላለፍ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ተናገሩ

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ችግር ለተራዘመ ጊዜ የሚቀጥል ከሆነ እና በምርጫ ቦርድ ስራ ላይ እንቅፋት ከፈጠረ የመጪው ምርጫን ዕጣ ፈንታ ለመወሰን ውይይት እንደሚካሄድ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን የተናገሩት የኮሮና ቫይረስን አስመልክቶ ዛሬ አመሻሽ ላይ በሰጡት መግለጫ ነው። 

የኮሮና ቫይረስ በመጪው ምርጫ ላይ ተጽዕኖ ያሳድር እንደው ለመለየት ምርጫ ቦርድ የራሱን ጥናት እየሰራ እንደሚገኝ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የቦርዱን ጥናት መሰረት አድርጎ ውሳኔ እንደሚተላለፍ አመልክተዋል። የመጨረሻ ውሳኔው ይፋ የሚደረገውም “የጋራ ስምምነት” ከተደረሰበት በኋላ እንደሚሆን በሀገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ “በሰበር ዜና” በተላለፈው መግለጫቸው አስታውቀዋል። 

“በቻይና እንዳየነው አይነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሄንን ጉዳይ መቆጣጠር፣ ማለፍ የሚቻል ከሆነ በአሰብነው እቅድ መሰረት መሄዱ ተመራጭ ቢሆንም ምናልባት ለተራዘመ ጊዜ ችግሩ የሚቀጥል ከሆነ እና ምርጫ ቦርድ ስራውን መከወን የሚቸገር ከሆነ፤ በሚያደርጉት ጥናት መሰረት ውይይት የሚደረግ ይሆናል” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። 

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በሀገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ “በሰበር ዜና” በተላለፈው መግለጫቸው የኮሮና ቫይረስ በምርጫ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖን በተመለከተ ምርጫ ቦርድ የራሱን ጥናት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።  የቦርዱን ጥናት መሰረት አድርጎም ውሳኔ እንደሚተላለፍ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ምሽቱን ባወጣው መግለጫ የኮሮና ቫይረስ ለሳምንታት አሁን ባለበት ሁኔታ ከቀጠለ በምርጫ ኦፕሬሽን ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ማረጋገጫ ሰጥቷል። ምርጫ ቦርድ በቫይረስ ምክንያት ተጽዕኖ ሊደርስባቸው ያላቸው “ከፍተኛ የሰው ዝውውር ያሳትፋሉ” በሚል የገለጻቸውን “የመራጮች ትምህርት፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች ስልጠና እና የቁሳቁስ ስርጭትን” ነው። 

በእነዚህ ተግባራት ላይ የሚደርስ መስተጓጎል በመራጮች ምዝገባ ዝግጅት ላይ ተጽእኖ እንደሚያስከትል ቦርዱ ዛሬ ለውይይት ለጠራቸው የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ገለጻ አድርጓል።  ገዢው የብልጽግና ፓርቲን ጨምሮ 45 የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደተሳተፉበት በተገለጸው በዚህ ውይይት የኮሮና ቫይረስ በምርጫ ኦፕሬሽን ስለሚኖረው ተጽዕኖ እና ሊወሰዱ ስለሚችሉ አማራጭ እርምጃዎች ውይይት መደረጉን ቦርዱ አስታውቋል።

የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ  በምርጫው ዝርዝር አፈጻጸም እና በጊዜ ሰሌዳው ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ ለመገምገም፤ ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር ተከታታይ ውይይት በቀጣይም እንደሚያደርግ ቦርዱ ገልጿል። (ኢትዮኢሌክሽን) 

የምርጫ ክልሎች ካርታ ይፋ ተደረገ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልል ካርታን ዛሬ ይፋ አድርጓል። በዛሬው ስነ ስርዓት ላይ የሀገር አቀፍ፣ የዘጠኙ ክልሎች እንዲሁም የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች የምርጫ ክልል ካርታዎች ለዕይታ በቅተዋል።

በአዲስ አበባው ሃያት ሬጀንሲ ሆቴል በተካሄደው በዚሁ ስነ ስርዓት ላይ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ የምርጫ ክልሎች ካርታን በተመለከተ በመስሪያ ቤታቸው ስለተደረገው ዝግጅት ማብራሪያ ሰጥተዋል። “አሁን የምርጫ ቦርድ ያደረገው የምርጫ ክልልን እንደገና ማካለል ወይም ማሻሻል አይደለም። ተበታትኖ የነበረውን የቃላት የካርታ መረጃ፤  በዘመናዊ መልክ አሰናድቶ፤  ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ካርታነት መለወጥ ነው” ሲሉ ለተሰብሳቢዎች አስረድተዋል። 

በስነ ስርዓቱ ላይ የህግ ምሁሩ ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ “የምርጫ ክልሎች አከላለል መርሆዎች እና ህጋዊ ማዕቀፉን” የተመለከተ ገለጻ አቅርበዋል። የምርጫ ክልል “የሕዝብ ተወካዮች የሚመረጡበት፣ የተወሰነ የህዝብ ቁጥር የያዘ፣ ተለይቶ የሚታወቅ እና ከሌሎች የምርጫ ክልሎች ጋር የሚዋሰን አካባቢ” እንደሆነ ገልጸዋል። በአንድ የምርጫ ክልል እንደ የሀገሩ ሁኔታ አንድ አሊያም ሁለትና ከዚያ በላይ ተወካዮች ሊመረጡ እንደሚችሉም ጠቁመዋል። 

“አንድ የምርጫ ክልል ምን ያህል ህዝብ ነው መያዝ ያለበት?” የሚለው አለም አቀፍ መለኪያ ማስቀመጥ እንደማይቻል ዶ/ር ጌታቸው ተናግረዋል። በአሜሪካ የምርጫ አወካከል 800 ሺህ ህዝብ አንድ ተወካይ እንዳለው ያስታወሱት የህግ ምሁሩ አሁን ባለው የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት አንድ ተወካይ ስንት ሰዎች መወከል ይገባው እንደነበር ጥቆማቸውን አቅርበዋል። በኢትዮጵያ ህገ መንግስት የተቀመጠው የፓርላማ መቀመጫ ብዛት 550 መሆኑን የጠቀሱት ዶ/ር ጌታቸው መቀመጫው ለህዝብ ብዛት ሲካፈል፣ አንድ ተወካይ ከ180 ሺህ እስከ 190 ሺህ ሊወክል ይገባው እንደነበር ስሌቱን አስቀምጠዋል። 

የምርጫ ክልሎች አከላለል ታሪካዊ ዳራን ያብራሩት የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዋ 100 ሺህ የሚደርስ የህዝብ ብዛት ያላቸው እንደ አንድ የምርጫ ክልል ይወሰዱ እንደነበር ገልጸዋል። የዚህንም አፈጻጸም ሲፈትሹ ችግሮች እንደታዩበት አስረድተዋል። የምርጫ ክልሎች የተካለሉት ለህገ መንግስት አጽዳቂ ጉባኤ ዝግጅት በተቋቋመ ግብረ ኃይል በ1985 ዓ.ም. እንደነበር የተናገሩት ብርቱካን ሚደቅሳ ያለፉት አምስት ምርጫዎች የተካሄዱት ግብረ ኃይሉ ባካለላቸው 547 የምርጫ ክልሎችን እንደሆነ አመልክተዋል። ግብረ ኃይሉ የምርጫ ክልሎችን ለማካለል የተጠቀመው የህዝብ ቆጠራ ውጤት ግን በደርግ ጊዜ በ1976 ዓ.ም. የተደረገውን ነበር ብለዋል።   

ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሎችን እንደገና እንዳላካለለ የተናገሩት ብርቱካን ሚደቅሳ የዘንድሮ ምርጫ በቀድሞዎቹ የምርጫ ክልሎች እንደሚካሄድ ግልጽ አድርገዋል። የምርጫ ክልሎችን እንደገና ማካለል ወይም ማሻሻል ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ መጽደቅ እንዳለበት፤ ይህም ስድስት ወር ሊወስድ እንደሚችል ያነሱት የቦርድ ሰብሳቢዋ ምርጫውን በጊዜ ለማካሄድ እንደማያስችል አስረድተዋል። የህዝብ እና ቤት ቆጠራ በወቅቱ አለመካሄዱም እንደገና ላለማካለሉ ሌላው ምክንያት እንደሆነ አብራርተዋል። 

በስነ ስርዓቱ ላይ ተሳታፊ የነበሩ ፖለቲከኞች ከምርጫ ክልሎች ጋር የተያያዙ ጥያቄዎች አቅርበዋል። የኦጋዴን ብሔራዊ ነጻ አዉጪ ግንባር (ኦብነግ) ስራ አስፈጻሚ አባል ሀሰን ሙአሊም፤ የምርጫ ክልል ካርታው የሶማሌ ህዝብ ክልልን በሚመጥን መልኩ እንዲሻሻል ሀሳብ አቅርበዋል። ሌላ ተሳታፊም “የክልሎችን የካርታ ወሰን የጠበቀ አይደለም” ብለዋል።

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ ምርጫ ቦርድ የቆየ መረጃ ለምን ተጠቀመ? ብለዋል። አቃቂን በምሳሌነት በማንሳት በፊት በአንድ ክልል የነበሩ ወደ ሌላ መካተታቸውን አንስተዋል። በምርጫ ክልል ካርታዎች ውስጥ ሲዳማ በክልልነት ለምን እንዳልተካተተም ጠይቀዋል።

የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዋ “የሲዳማ የክልልነት ጥያቄን በተመለከተ ምርጫ ቦርድ ስራውን ጨርሷል። የስልጣን ርክክቡ ተፈጽሞ፤ ሲዳማ ክልል መሆኑ formalize ካልተደረገ፤ ለፓርላማ መቀመጫ ቆጥረን ማቅረብ አይጠበቅብንም። ብናደርግም ስህተት ነው” ሲሉ መልሰዋል። 

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ ዛሬ ይፋ በተደረገው የምርጫ ክልሎች መሰረት በሁሉም ቦታዎች ምርጫ ይካሄድ እንደው ጠይቀዋል። ብርቱካን ሚደቅሳ ለጥያቄው በሰጡት ምላሽ” ‘ምርጫ በዚህ ቦታ አይደረግም’ ብለን የያዝነው የምርጫ ክልል የለንም። በሀገሪቱ በሙሉ ለማከናወን ነው ያቀድነው። ከባድ ጎርፍ፣ እሳት፣ ከባድ የጸጥታ ችግር፤ ምርጫ ለመከወን ካስቸገረን፤ የዚያን ጊዜ የምናየው ይሆናል” ብለዋል። 

በዛሬው የምርጫ ክልል ካርታ ይፋ ማድረጊያ ስነ ስርዓት ላይ አቶ ዳውድ ኢብሳ፣ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና፣ አቶ ጀዋር መሐመድ፣ አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋን ጨምሮ ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮችም ተገኝተዋል። (ኢትዮኢሌክሽን)

በምርጫ ቦርድ ቀነ ገደብ የተመዘገቡ አዲስ ፓርቲዎች ስድስት ብቻ ናቸው

  • አራት የፓርቲዎች ስብስቦች የቅንጅት ጥያቄያቸውን ለቦርዱ አቅርበዋል 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በምርጫ መሳተፍ ለሚፈልጉ አዲስ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሰጠው ቀነ ገደብ ውስጥ የተመዘገቡት ስድስት ብቻ መሆናቸውን ገለጸ። የቅንጅት መመስረቻ ማመልከቻቸውን በቀነ ገደቡ ያሳወቁ የፓርቲ ስብስቦች አራት ብቻ መሆናቸውንም ጨምሮ አስታውቋል። 

የሃያ ሁለት አዲስ ፓርቲዎችን የምዝገባ ማመልከቻ እየተመለከተ የሚገኘው ምርጫ ቦርድ በመጪው ምርጫ ለመወዳደር ለሚፈልጉ ተመሳሳይ አመልካቾች እስከ ትላንት ሰኞ፣ የካቲት 30፣ የሚቆይ ቀን ገደብ ሰጥቶ ነበር። ቦርዱ ቀነ ገደቡን ያስቀመጠው “ለመጪው ምርጫ ፓርቲዎችን ብቁ የማድረጉ ስራ ጊዜ የሚወስድ” መሆኑን በምክንያትነት ጠቅሶ ነው።

በምርጫ ቦርድ ቀነ ገደብ መሰረት የሚጠበቅባቸውን ሰነዶች አሟልተው ለመስሪያ ቤቱ ያስገቡ ስድስቱም አዲስ ፓርቲዎች በክልል እና ከተማ ደረጃ የሚንቀሳቀሱ እንደሆኑ ከቦርዱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። በክልላዊ ፓርቲነት ለመመዘገብ ማመልከቻቸውን ያስገቡት በሶማሌ፣ ቤንሻንጉል፣ አፋር እና አማራ ክልሎች እንደዚሁም በድሬዳዋ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ናቸው።

ምርጫ ቦርድ ከየካቲት 30 በኋላ የምዝገባ ማመልከቻቸውን የሚያስገቡ አዲስ ፓርቲዎች ከመጪው ምርጫ ውጪ እንደሚሆኑ ቀደም ብሎ ማስጠንቀቁ ይታወሳል። ቦርዱ ግንባር አሊያም ቅንጅት መመስረት ለሚፈልጉ ፓርቲዎችም ተመሳሳይ ቀነ ገደብ ሰጥቶ ነበር።

የቀነ ገደቡ ዕለት ሳያልፍ የቅንጅት ማመልከቻቸውን ለመስሪያ ቤቱ ያስገቡ የፓርቲዎች ስብስቦች አራት ብቻ መሆናቸውን ቦርዱገልጿል። መቀናጀታቸውን ለምርጫ ቦርድ ካሳወቁት ውስጥ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና አፋር ክልል ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ይገኙበታል። “አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት” የተሰኘው የሶስት ሀገር አቀፍ ፓርቲዎች ስብስብም ለቦርዱ የቅንጅት ጥያቄ ካቀረቡት መካከል መሆኑን ቦርዱ አረጋግጧል።    

“አብሮነት” በተሰኘው መጠሪያ የሚታወቀውን ይህን ቅንጅት የመሰረቱት የኢትዮጵያዊያን ሃገር አቀፍ ንቅናቄ (ኢሃን)፣ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) እና ኅብር ኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኅብር-ኢትዮጵያ) የተባሉት የፖለቲካ ፓርቲዎች ናቸው። ፓርቲዎቹ በመጪው አገራዊ እና ክልላዊ ምርጫ በሀገር አቀፍ ደረጃ ተቀናጅተው ለመስራት መስማማታቸውን ለቦርዱ ባስገቡት ማመልከቻ ላይ ጠቁመዋል።

ከቀነ ገደቡ ሶስት ቀናት አስቀድመው መቀናጀታቸውን ይፋ ያደረጉት ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ (ባልደራስ) እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅትም (መኢአድ) ማመልከቻቸውን ለቦርዱ አስገብተዋል። “ባልደራስ መኢአድ” የሚል መጠሪያ እንደሚጠቀሙ ያስታወቁት ፓርቲዎቹ በመጪው ምርጫ፤ አዲስ አበባን ጨምሮ በመላ ሀገሪቱ፤ በጋራ የምርጫ ማኒፌስቶ እና ምልክት እንደሚወዳደሩ አስታውቀዋል። (ኢትዮኢሌክሽን)